Monday, March 14, 2011
Friday, March 4, 2011
Wednesday, March 2, 2011
KING ( ከዲያቆን አሸናፊ)
ይቅርታ (ክፍል1)
ዘመድ አዝማድ የተወን ጓደኛ ወዳጅ ገሸሽ ያለን ሆነን ይሆናል። በማግኘታችን የከበቡን ሰዎች ዛሬ ስናጣ ተበትነው ይሆናል። በሐሰተኛ ምስክሮች የማይገባንን ፍርድ ተቀብለን ይሆናል። ቅንዓታቸውን ሃይማኖትና ፍትህ አልብሰው በሚታገሉ ሰዎችም የመጠላት ቀንበር ወድቆብን ይሆናል። የሳምናቸው ነክሰውን የቀረብናቸው ገፍትረውን አበባ የሰጠናቸው አፈር በትነውብን ወርቅ ያበደርናቸው ጠጠር መልሰውልን እህል የሰጠናቸው አፈር ሰፍረውልን ይሆናል በእኛ ምክንያት የተገኙ ሰዎች በራሳችን ላይ የሚፈነዱ የቡድን አደጋዎች ሆነውብን ይሆናል።
ፈርጅ ብዙ በሆነችው እድሜ ተለሳልሰው ገብተው በቤታችን ከተደላደሉ በኋላ በማያቋርጥ ሙግት አድክመውን ይሆናል ። አደራ ብለን የሄድነውን ትዳራችንን ንብረታችንን ባልንጀሮቻችን ወርሰው ተቀምጠው ይሆናል። ችግራቸው እስኪያልፍ ተጠግተውን ሲያገኙ ተረከዛቸውን አንሥተውብን ይሆናል። አጥንት በሌለው ምላሳቸው አጥንታችንን ሰብረውት በመርዛም ቃላቸው ሕሊናችንን ጎድተው ይሆናል አልመው ቁስላችን ላይ የወረወሩት ቀስት ዛሬም እያመረቀዘ ይሆናል ለእነርሱ ክፉ እንዳልሆንን እያወቁ ከጠላት ጋር ጉድጓድ ምሰውልን ይሆናል።
በሰው ውድቀት የሚረካው ያው ሰው በሆነባት ዓለም በከሰረው ንግዳችን በፈረሰው ትዳራችን የለመጠን ተደስተው ይሆናል። ፍቅራቸውን ነርበን ስንሄድ እንደ ረሃብተኛ እንጀራ አቅርበው ሸኝተውን ይሆናል። ሰዎች እንደጥንቱ አልሆን ብለውን ተለዋውጠውብን ይሆናል። ድሮ የሚያዳምጡን ሰዎች ዛሬ ቃላችን እሬት ሆኖባቸው እንደ ሸንኮራ አገዳ መጠው የጣሉን ሰዎች ሆነን ይሆናል። ሳንፈለግ ያለልክ አክብረውን ጊዜያቸው ሲያልቅ ደግሞ ስማችንን በምናልፍበት ሁሉ አጥፍተውት ይሆናል። ከክርስቲያን የማይጠበቅ ነገር አድርሰውብን ይሆናል። አዎ በሆሳዕና ማግስት ስቀለው ስቀለው መባል ያሳዝናል። እንደ አሚና (ላሊበላ) በእኛ ተዝካር ላይ ስለሚዳሩ ሰዎች ስናስብ ሕሊና ይቆስላል። የማይዋደዱ ሰዎች እኛን ለማጥፋት ሕብረት ሲፈጥሩ ማየት ያርዳል። መምሸቱን ሳያረጋግጡ ገና ፀሐይዋ ቆልቆል ስትል ተሰናባቹ ሲበዛ ዱዳ ያደርጋል። ወዳጅ በገንዘብ ሲለወጥ ማየት በሕሊና ቀርቶ በገንዘብ ማሰብ ሲጀመር ከማን ጋር ነበርኩ? ያሰኛል። ዛሬ በር ዘግተን የከተማ መናኝ መሆናችን ዝምታን መርጠን እንደማይደንቀው ፀጥ ማለታችን ሰው የማይለምድ አውሬ ነው ብለን መናገራችን ከሰው ጋር ከመኖር ከክርስቶስ ጋር በዱር መኖር ይሻላል ማለታችን ከመቼውም ጊዜ ይልቅ በሰው ጠባይ ተስፋ መቁረጣቸውን ለትችት አያስቸኩለንም።
በሄዱት ሰዎች እየተበሳጨን ያሉትን ማመን አቅቶን ይሆን? አሁን ባጠገባችን ያሉት ወዳጆቻችን በእውነት የሚወዱን ልበ ልቡናችን እየነገረን ነገር ግን ከጉዳችን የተነሣ ማንንም ላለማመን ምለን ይሆን? አገር አልባ ያደረጉንን ከምንወደው ወገን የለዩንን ፍቅራችንን በአመድ ያዳፈኑትን መርሳት ቸግሮን ይሆን? ኑሮአችንን የዕንባ ያደረጉትን ለጨጓራ ለደም ብዛትና ለማድያት ያበቁንን መተው መሸነፍ መስሎን ይሆን? እኛን የሚበላ እሳት የሚሞቁትን አይቶ እንዳላየ ማለፍ የማይሆንለት ሆኖብን ይሆን?
ውድ አንባቢ ሆይ! እናንተን የሚሰማችሁ ህመም ለዘመናት ተሰምቶኛል። ራሴን አሸንፌ የይቅርታ ሰው ለመሆን ለብዙ ጊዜ ከራሴ ጋር ታግያለሁ። መራራነት እጅግ ጎድቶኝ አይቻለሁ። ስለ ይቅርታ ብዙዎች መክረውኝና ብዙ ምክር ሰምቼ መመለስ አቅቶኝ እንደነበር አስታውሳለሁ። አንድ አባት ግን በመጨረሻ <<ለሰይጣን እንኳን ቂም በቀል የለንም አልገዛልህመ የሚል እምቢታ እንጂ ለገዛ ወንድምህ ግን ቂመኛ በመሆንህ እራስህን ልትታዘብ ይገባል ይልቁንስ ዛሬውኑ ዳንና ሂድ>> ሲሉኝ ትልቅ ቀንብር ከላዬ ወደቀ።
ከዚህ ሁሉ በላይ የይቅርታን ሕይወት ካልተለማመድን እግዚአብሔርን አባት ብሎ ለመጥራት እንደማልችል ሲገባኝ ችሎታውን እንዲሰኝ እየለመንኩ በታላቅ ንስሃ በፊቱ ወደቅሁ። አስቀየሙኝ የምላቸው ሰዎች ስም እየጠራሁ ስጸልይላቸው ቅሬታዬ እየተቀረፈ ወደቀ። ስናገር ይቀለኛል የሚለውን መመሪያ ጥዬ በደላቸውን ማውራት ሳቆም በዝምትአ ሃይል አገኘሁ።
ይቆየን. . .
Tuesday, March 1, 2011
KING ( ከዲያቆን አሸናፊ)
ሰውዬው መሣርያውን አስተካክሎ ሰው ሊገል በጠዋት ከቤቱ ሲወጣ ሚስቱ "ቡና ፈላ ወይ?” ብትለው “ምነው በዓርብ ምድር” ብሎ ደነገጠ ይባላል። በአገራችን ሃይማኖት ባህል ሆኗል። የታወቁ ሽፍቶችና ነፍሰ ገዳዮች ዳዊት ደጋሚ እንደነበሩ እንሰማለን። በጎንደር አንድ ሽፍታ ዳዊት ሲደግም ተከታዮቹ ከፊቱ ቆመው አንድ ሰው እያለፈ ነው ምን እናድርገው? ቢሉት በመናገር ጸሎቱ እንዳየታጎል ፈርቶ እጁን በአንገቱ ላይ በመገዝገዝ ግደሉት አላቸው ይባላል።
ሕዝባችን ለእግዚአብሔር በሙሉነት መታዘዝ የመነኮሳትና የቀሳውስት ተግባር ስለሚመስለው እርሱ ያሻውን እየፈጸመ የወከላቸው ቀሳውስት እንዲተጉለት የጥምጥም በመስጠት ተረጋግቶ የተቀመጠ ነው። ይቅርታ ባህላችን አይደለም። ባህላችን ክስ በቀል ነው። በገጠሩ የማያባራ ጠብ አለ እስከ ሰባት ዘር ቆጥረው ይጫረሳሉ። ሕዝባችን ለደም እንግዳ አይደለም። የከተማውም ሰው በሃሜት በአድመኝነት በሰው እንጀራ በመግባት . . . ተዳድፏል። በአሁኑ ወቅት በዙ ሰው የሥጋ ጤና የአእምሮ ሰላም የለውም። ትልቁ ችግር ግን ይቅርታ ማጣት ነው።
በአንድ ነጭ ወረቀት ላይ በብዕር አንድ ነጥብ አስቀምጠን ምን ይታያችኋል? ብለን መቶ ሰው ብንጠይቅ ሁሉም አንድ ጥቁር ነጥብ ይታያችኋል። ትልቅ የሆነው የወረቀቱ ንጣት ማንም አይታየውም። አንድ ነትብ ግን ሁሉም ይታየዋል። ስህተት በሚፈልግ ዓይን እንድንኖር የእግዚአብሔር ፈቃድ አይደለም።
የታሪክና የሥነ መለኮት መጻሕፍትን ማዘጋጀት ቀላል ነው። ድካም እንጂ ውስጣዊ ጥያቄ የለበትም። ይቅርታን ለመጻፍ ግን ሕይወቴ ከገለባ ይልቅ እስኪቀለኝ በሚዛን ላይ ወጥቻለሁ ። ስለዚህ ብዕሬን አስቀምጬ ራሴን ለረጅም ጊዜ አየሁት። የእግዚአብሔር እጅ ከሌለበት ጣዕም የሌለውን እንዲህ ያለውን ሥራ ለመሥራት ለእግዚአብሔር መሸነፍን መረጥኩ የበደለልኳቸውን ሰዎች የቻልኩትን በአካል ያልቻልኩትን በደብዳቤ ይቅርታ ጠየቅሁ። የበደሉኝ የሚመስለኝ ሰዎችም ለይቅርታ ሲደነድኑ በደሉ የእኔ ነው ብዬ እግራቸው ላይ ስወድቅ ሊገለጽ በማይቻል የፍቅር ኃይል በዕንባ ሲወድቁ አየሁ። ለመሄድ ዳር ዳር ለሚሉት ወዳጆአህም ሁልጊዜ እንደ እንደምወዳቸው የሚገልጽ የመሸኛ ደብዳቤ ሰሰጣቸው እስከ ጊዜው በደስታ ሄዱ።
ይቅርታ ለሰዎቹ ጥቅም ከፈለኩት ይልቅ ያለ ይቅርታ በሕይወት እንደማልቆይ በተከታታይ ከገጠሙኝ በሽታዎች ተረድቻለሁ። ችግሬ በነጻ ማፍቀር አለመቻሌ ነው። የሰው መርህ <<ሰጥቶ መቀበል>> ነውና። የእግዚአብሔር ስጦታ ግን <<ነጻ ስጦታ ነው>> ቢሆንም ይቅርታ የሚያደርግ እንጂ የረጋ ነገር እንዳልሆነ ስረዳ ዛሬም ወደ ይቅርታ ፍጻሜ መሄድን እናፍቃለሁ።
ይቆየን ዲ. አሸናፊ
KING ( ከዲያቆን አሸናፊ)
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!
በገጠሩ የአገራችን ክፍል ሁለት በተለያየ ስፍራ የሚኖሩና ደም የተቃቡ ሰዎች ቂመኞች በመሆናቸው ሁልጊዜ በዓይነ ቁራኛ እየተጠባበቁ ነው የሚኖሩት። በአጋጣሚ እነዚህ ሁለት ጠበኞች ቤተ ከርስቲያን ለመሳለም መጥተው ከበር ላይ ከተገናኙ ወደ ውስጥ ከመግባታቸው በፊት ቂምህን አውርድ በመባባል የታጠቁትን መሣሪያ ከበር ላይ አስቀምጠው ይገባሉ። ሲወጡ ደግሞ ቂምህን አንሣ ተባብለው መሣሪያቸውን አንሥተው በዓይነ ቁራኛ እየተያዩ ይለያያሉ። ለእግዚአብሔር ክብር ቢኖራቸው ግን ይቅር በተባበሉ ነበር። ቀሳውስቱም ከነቂማቸው ሲቀድሱ ግድ የላቸውም ያልበደልን ጫማ ለማስወለቅ ግን ይታገላሉ።
ጾም ጸሎት ምሕላ ማድግ የተለመደ ነው። እነዚህ በመንፈሳዊው ዓለም እንደ አስቸኳይ ጊዜ አዋጅ የሚቆጠሩ ናቸው። ግን ሦስት ነገሮችን ማሟላት አለባቸው። እነርሱም የጸሎት ርእስ ማየዝ እርስ በርስ ይቅር መባባልና ንስሓ መግባት ናቸው። አሊያ ዓለማ የሌለው ጾም ጸሎት ወይም ምሕላ ይሆናል ማለት ነው። ጾም ጸሎት ምሕላው ይደረጋል እንጂ በረከቱ ግን የለም። ከሚሰማ አምላክ ጋር እየተነጋገርን ለምን አልመለሰልንም? ብለን አንጠይቅም። በአገራችን ሃይማኖት ባሕል እንጂ ሕይወት አይደለምና።
የሀገራችን ሰው ችግሩን አላወቀም። እንጀራ የነሳው በሃዘን ጨለማ ያስቀመጠውን ድሪቶ ያስለበሰውን የጎረቤት ተንኮል ይመስለዋል የገዛ ሃጥያቱ መሆኑን ግን አላወቀም። ስለዚህ ምድሪቱ ፈውስ እንድታገኝ የሃዘን ማቋን እንድታወልቅ በምድሪቱ ላይ ብሔራዊ ንስሓና ይቅርታ ያስፈልጋል። ይህንን ንስሓና ይቅርታ ቤተ ክርስቲያን በተሰበረ ልብ ተቀብላ ለሕዝብና ለመንግሥት ካልገለጠች ከቤቱ የሚጀምረው የእግዚአብሔር ቁጣ ፈጥኖ ያገኛታል።
አገራችን ኢትዮጵያ የሦስት ሺህ ዓመት ታሪክ ያላት አገር ናት። በእውነቱ ስናየው ግን ሦስት ሺህ ዓመት የደም ታሪክ ነው። ሰው ሰውን ገድሎ ጀግና የሚባልበት እኔ የማክሰኞ ገዳይ እኔ የሐሙስ ገዳይ እየተባለ የሚሸለልበት ምድር ናት። እግዚአብሔርም በብዙ መንገድ ቢቀጣትም ልብ ደንዳናዋ አገር አልሰማችም።
መጦር ስትችል የሰማንያ ዓመት ሽማግሌና ከሃምሳ ዓመት በላይ የገዙ ንጉሷን ገድላለች። ጳጳሷንም ገድላ ዘፍናለች። ታላላቅ ሚኒስትሮቿን ስድሳውን በአንድ ጉድጓድ ቀብራለች። ከዚህ ጊዜ ጀምሮ መሪና ጳጳስ የሚሰደድባት አገር ሆናለች። ያሉትንም ለማሳደድ የተጠማችው ምድር ራሷን አይታ ንስሓ ለመግባትና ይቅር ለመባባል ገና አልተዘጋጀችም።
የዓለም ሁሉ ትዝብት የሆነችው አገር ያለ ንስሃ ይቅርታ ከረሃብ መዝገበ ቃላት ከውድቀት ስፍራዋም አትነሳም። ማወቅ ዕዳ የሆነባት አገርና ቤተ ክርስቲያን መፍትሔአቸው ብሔራዊ ንስሓ ነው። የእግዚአብሔር እጅ ጣልቃ ባይገባ ብዙ ጊዜ ወደ ዘረኝነት ጭፍጨፋ ልናመራ የቃጣን ሕዝቦች ነን። ግን በዚሁ በከተማችን ስለሩዋንዳ የዘር እልቂት ሻማ ለኩሰን ዞረናል። ዛሬም የምናዝነው ምኞታችን ባለመፈጸሙ እንጂ እግዚአብሔርን በመግፋታችን አይደለም።
ይቅርታ እውቀት ሳይሆን መታዘዝ ነውና ይቅር ተባባሉ። አገሬንና ቤተ ክርስቲያኔንም ለይቅርታ እማፀናለሁ።
ይቆየን…ዲ.አሸናፊ
Subscribe to:
Posts (Atom)