Sunday, February 27, 2011

KING ( ከዲያቆን አሸናፊ)

የተቀያሚ ሰዎች ባሕርይ

1.     የደረሰባቸውን በደል ድንገተኛ መሆኑን ከመቀበል በፍቅራቸው ወራትም ሲዘጋጅ እንደነበረው ያስባሉ።  ነገር ግን ፍቅርና ጠብ ለየብቻ እንደሚኖሩ ሊያስቡ ይገባል።  ብርሃንና ጨለማ በአንድ ጊዜ አይወጡምና።

2.    የራሳቸውን ቅንነት ያስባሉ እንጂ ያን ሰው ሳያውቁ ሊበድሉት እንደሚችሉ ስለሚረሱ ጥፋቴ ምንድነው? አይሉም።  የሚያስደንቀው ብበድለውስ እንዴት ይርቀኛል? ሲሉ ይቅርታ ለማድረግ ግን ፈቃደኛ አይደሉም።

3.    ሰዎችን ለመቀየም ምክንያት ይፈልጋል።  ከሰው ጋር ስንኖር አነዱ ዓይን ስህተትን ሲያይ አንዱ እየሸፈነ መሆን አለበት።

4.    አንዴ ከተቀያየሙ በኋላ ዋጋ እንደሌለው ያምናሉ።  በዓለም ላይ ግን ከተሰበረ የማይጠገን ሞት ብቻ ነው።  ደግሞም እኛ የእግዚአብሔርን ይቅርታ የፈለግነው ለአንድ ጊዜ ብቻ አይደለም።

5.    ነገሮችን በትክክለኛ መጠናቸው ሳይሆን አጋነው ይመለከታሉ።  ስድብን አቅም ቢኖው ገድሎኛል በማለት ይለጥጡታል።  የትክክለኛ ሰው ባሕርይ በደልን ሳይሆን ፍቅርን አብልጦ የሚያይ ነው።

6.    ቂምን መርሳት ለወደፊቱ አለመጠንቀቅ ይመስላቸዋል።  ሰውን ግን ከጥርጣሬው ይልቅ ቅንነቱ ይጠብቀዋል።  ተጠራጣሪዎች እራሳቸውን ቢጠብቁም የሚፈሩት አይቀርም።  እግዚአብሔር ግን ቅኖችን ይጠብቃል።  

7.    ይቅር ማለትን እንደመሸነፍ ይቆጥሩታል።  የምንኖረው ግን ክፉውን ለማሸነፍ ለመልካም ነገር በመሸነፍ ነው።  ልይቅርታ መሸነፍ ለእግዚአብሔር መሸነፍ ነው።

8.    የእግዚአብሔር ምስጋና ይረሳሉ።  መትረፋቸው ለምስጋና አያበቃቸውም መሞከሩ ግን ይቆጫቸዋል። እግዚአብሔር ካልጣለን በሰው መቀየም ከንቱ ነው።

9.    ከተደረገላቸው በጎ ነገር ይልቅ የተደረገባቸውን ክፉ ነገር አትኩረው ያየሉ።  ከ90% መልካም ነገር ለ10% ስህተት ዋጋ ይሰጣሉ።  ክፋትን የሚጠብቁ ሰዎች መልካም ነገር ቢበዛም ደስታቸው በደልን በመመዝገብ ነው።  ይህ ደሞ ስይጣንነት ነው።

10.  ጥንካሬ የሌለው ሞራል ስላላቸው በትንሽ ነገር ይቀየማሉ።  እኛ ሰው ነን እንጂ እንደ ውሻ ፊት እያየን የምንኖር አይደለንም።

11.    ማንም ሰው ድካም ስላለበት የሚሸከመውን ምሥጢሩን የሚጠብቅለት ይፈልጋል።  ቂመኞች ግን ሰው ስለሚርቃቸው ብቸኛ ይሆናሉ።

እንግዲህ የምንኖረው ከሰው ጋር እንጂ ከመላእክት ጋር አይደለምና የይቅርታ ሰው ልንሆን ይገባል።  ስንቱን ተቀይመን እንዘልቀዋለን? ሁሉም ደከማ ነውና።


የይቅርታ ሰው ለመሆን
1.     ከእግዚአብሔር በየዕለቱ ይቅርታ ፈላጊዎች መሆናቸውን ማሰብ፡

2.    እልከኝነት ልባችንን በቃሉ መገሰጽ

3.    እግዚአብሔር ካሳየን ምህረት እንጻር የወገኖቻችን በደል ምንም መሆኑን ማሰብ።

4.    እነርሱ ልንበድላቸው የምንችለውን እኛን በደሉ እኛ ግን መልካሙን እግዚአብሔርን የበደለን መሆናችንን ማሰብ፡

5.    ጠቡ የመጣው ከፍቅር በኋላ ነው፡ ስለዚህ መነሻ ዓላማችን ፍቅር እንጂ ጠብ እንዳልነበር ማሰብ።

6.    ከሁሉም በላይ ለተቀየምናቸው ሰዎች መጸለይ ጥላቻን ይቀንሳል።  ጸሎትም የክርስቶስን ፍቅር በልባችን ያፈሳል።  ለሰይጣን እንኳን ቂም በቀል የለንም አግንቼ እንዲህ ባረግኹት አንልም አልገዛልህም የሚል እሚቢታ እንጂ።  ለገዛ ወንድማችን ግን ቂም በቀል ያለን በመሆናችን ራሳችንን ልንታዘብ ይገባል።


ይቆየን(ዲ.አሸናፊ)

Saturday, February 26, 2011

KING ( ያልፋል ከዲያቆን አሸናፊ መኮንን)


ያልፋል
                                       
ሰውዬው ምንም ቢደርስበት “ይህም ያልፋል” በማለት የሚጽናና ነበር በዚህ ምክንያት ስሙ “ይህም ያልፋል” ሆነ።  ይህ ሰው ኮት አፋፍ ላይ ደርሶ ሲያጣጥር ሳለ ወዳጆቹን ጠርቶ በመቃብሬ ላይ “ይህም ያልፋል” ብላችሁ ጻፉ በማለት ተናዘዘ።  እነርሱ ግን በጣም ተበሳጭተው “አላበዛኸውም ደግሞ ኪዚህ በኋላ ምንድነው የሚያልፈው?” አሉት።  ያ ሰውም ሞተ።  እነርሱም ቃሉን ለማክበር በመቃብሩ ድንጋይ ላይ “ይህም ያልፋል” ብለው ጻፉ።  ለካ በመቃብሩ ላይ መንገድ ያልፍ ኖሯል መቃብሩ በወሩ ፈጸ።  እነዚያ ሰዎችም እውነት ነው “ሁሉም ያልፋል” ብለው ተገረሙ።

ትውልድ አልፎ ትውልድ ተተካ።  ያለፉት የነበሩ አይመስልም።  ያሉትም የሚያልፉ አይመስልም።  ግን ቋሚ እግዚአብሔር ብቻ ሆኖ ሀሉን ያሳልፋል።  ብዙ ቆንጆዎች ረገፉ ውበት ሐሰት ደም ግባትም ከንቱ ነው የሰው ብርቱ የለውምና ብዙ ጀግኖች ሞቱ።  የነገስታት ክብር መቃብር ገዛው።  ፈላስፋዎች ሊቃውንቶች ስማቸው ብቻ ቀረ።  ጽዋ በሚዞርበት ዓለም በዙረቱ ስንቶች ደኸዩ ስንቶች ከበሩ!

በአንድ ሰርግ ላይ ሰባኪው ስለይቅርታ በአጽንዖት ሲያስተምር አንድ ሰው “ይቅር አልልም ቂም አይበሰብስም”  በማለት በድፍረት ሲናገር ሰምቻለሁ።  ዛሬ መሸነፍ መስሎን ይቅርታን ብንጠላም ቂምና በቀላችን የዛሬውን ስሜታችንን ያልፋል እንኳን ቂማችን እኛም እናልፋለን።  ሁሉም ሲያልፍ ይቅርታን መናፈቃችን አይቀርም።  ይህ ግን ነፍስን ለመጨበጥ እንደመሮጥ ነው።

በየመቃብሩ ይቅር በለኝ እያሉ መራራ ለቅሶ የሚያለቅሱ በአደባባይ በደላቸውን የሚናዘዙ በታለቅ ፀፀት የሚጮሁ ወገኖች ብዙ ናቸው።  ያ የጠሉት ሰው የሚሞት ስላልመሰላቸው ብዙ በደል አድርሰውበታል ወይም ይቅርታ ነፍገውታል።  በሞት ማለፍ የመጣ ቀን ግን የልመሰላቸው ነገር ሆኗልና ሰማይ ይጫናለቸዋል።  ከሰውዬው በደል በላይ የራሳቸው በደል ይታያቸዋል።  አይመለስምና መካስ አለመቻላቸው አይገኝምና አብረው መኖር አለመቻላቸው ያንገበግባቸዋል።  በእውነት ሁሉም ያልፋል።

አንዲት እናት ቤታቸው ለዘመናት ሰላም አጥቶ ሦስት ልጆች በተከታታይ ቀበሩ።  አራተኛዋ ልጅ ስትሞት በልቅሶ መሐል ተነሥተው የሞተችው የእኔ ልጅ ናት አታልቅሱብኝ ከእነዚያ ጋር ስንባላ በሞት አለፉ።  አሁንም አልተማርንም ነበርና ይህች የደረሰች ልጄ ሞተች።  ወገኖቼ “የቆመው ሳይዋደድ ለሞተው መናደድ” ምን ይጠቅማል?  ብለው እርቅ ወረደ።  አልቃሿ በቆመችበት ቦታ ሆና ስህተት የመሰላትን ትነቅፋለች::

“ምን ዘመን መጣብን ዘመነ መጋኛ
የታቀመመው አይድን ያለው አይስማማ”

ይህች አልቃሽ ሲሰገድላቸው የነበሩትን ንጉስ አውርዶ ለአብዮቱ ይጨፍርየነበረውን ወገን እነዲህ ብላ ገስጻዋለች፡-

“ዓለም ዋሾ ዓለም ወላዋይ
ከጃንሆይ ግቢ አልነበርሽም ወይ”

ሲያልፍ ሀሉም ነገር ይሰማናል።  ልናየው የጠላነው ሰው ሲርቅ ያባባናል።  ለሞት የተመኘነው ሲሞት ያስደነግጠናል።  ሙት አይወቀስም ብለን በክፉ እንኳ አናነሳውም በእውነት እንዲህ የሚያጨካክነን ዘላለም የምነኖር ስለሚመስለን ነው።  በሙሉ ልብ የሚያቆመን ይቅርታ እንጂ የዛሬው ጠንካራ ልብ አይደለም።  የናድነው ትዳር ያፈረስነው ባልንጀርነት የበጠስነው ፍቅር መነሻው መልካም እንደነበር ስናስብ ትዝታው ዕረፍት ይነሳናል።  ለወደፊቱ ከምናስቀምጠው በረከት ነው።  ይህችን ዓለም ለቀን ልንሄድ ስንል ሕይወትን ወደኋላ መልሰን ማየት ትርፉና ኪሣራችንን መተሳሰባችን አይቀርም።  ያን ቀን በዚህ ምድር ላይ ማንንም ለመጥላት አልኖርኩም ብለን ለራሳችን መናገር ስንችል ብቻ ሞትን በደስታ እንጋፈጣለን።

በሞትን ጊዜ ቂምና በቀላችን አብሮ ይቀበራል።  ሁሉም ነገር ይቀራል።  ዛሬ ከሰው ጋር የምንጣላው ስማችንን ስላጠፉት ነው።  ከሞትን ከጥቂት ደቂቃ በኋላ ግን “አስከሬኑ ታጠበ?” እንጂ “እገሌ ታጠበ?” አይሉንም።  ዕድሜ ልካችንን የኖርንለት ስማችን በጥቂት ደቂቃ ይጠፋል።  ለገንዘብ ስንል ወንድማችንን ለሞት እንመኘዋለን።  ነገር ግን ከሰበሰብነው ሀብት አእዱም ሳይከተለን ዓለምን ወደኋላ እምነትን ከፊት አድርገን እንጓዛለን።  የሰበሰብነው ንብረትም ለማናውቀውና ለማንፈልገው ሰው ይሆናል።  በእውነት ይህች ዕድሜያችን እንኳን ለጠብ ለፍቅርም አትበቃም።

አንድ ሰው እንዲህ ብሏል፡- ምንም ቢበድልህ የወንድምህን ሞቱን አትመኝ።  እርሱ ሞቶ አንተ አትቀርምና።  አንድ አባትም “ሟችም ገዳይም ሁለቱም ሟቾች ናቸው።  የቅደም ተከተል ጉዳይ ነው” ብለዋል፡፡

መሾምም መሻርም መከበርም መዋረድም መታመምም መወፈስም ማዘንም መደሰትም መታሰርም ነጻ መሆንም ማሸነፍም ማግኘትም ማጣትም መክነፍም መቀዝቀዝም ማበድም መረጋጋትም መወደድም መጠላትም መተኛትም መንቃትም መቀየምም መበቀልም ሁሉም ያለፋሉ።  በዚህ ወራጅ የሚል ድምፅ በበዛበት ዓለም የሚያረካን ነገር ቢኖር እግዚአብሔር ማለፍን ትልቅ ጸጋ አድርጎ መስጠቱ ነው።  ማለፍ ባይኖር የረገጠ ደስ እንዳለው የተረገጠ እንደከፋው በቀረ ነበር።  የበደል ንስሓ የሚገባው የተበደለ ለምስጋና የሚበቃው የማለፍ ሥርዓትን በሚሰራው በእግዚአብሔር ነው።  ይህንን ካየን የይቅርታ ሰው ለመሆን  የሚረዱንን ባሕርያት እናያለን።

ይቆየን
ወደፊት የተቀያሚ ሰዎች ባሕርይ ብልን እንመለከታለን

Wednesday, February 16, 2011

ሰውን የምንወደው ለጥቅም ነው።(King Nafkote)



በዚህ ምድር ላይ የሰው ልጅ ከሰው ልጅ ጋር ተስማምቶና ተዋዶ መኖሩ ሰብዕናው የቸረው ግዴታው ነው ሆኖም አመላችን እንደመልካችን ዝንጉርጉር ስለሆነ አንዱ አንዱን የሚወደው ከጥቅሙ አንጻር እንጂ እንዲሁ ከመሬት ተነስቶ አይደለም።

ብዙዎቻችን እስከ ዛሬ የኖርንበትን ሕይወት ወደኋላ ዘወር ብለን ብንመለከት ፍጹም ልንደነቅ እንችላለን።  ማናችንም ብንሆነ በዚህ ምድር ላይ የምንኖር ሰዎች በሕይወታችን ወደናቸው ያለፍናቸውን ሰዎች ወይም ዛርም ድረስ የምንወዳቸውን ሰዎች ብንመረምር ከነሱ በምናገኝ ጥቅም ወደድናቸው እንጂ እንዲሁ ዝምብለን አልወደድናቸውም።  በዚህ ዓለም እንዲሁ የሚወደን ወይም የወደደን አንድ ጌታ ብቻ ነው። በዚህ ዓለም የወለደችን እናታችን እንኳ አለአንዳች ጥቅም አትወደንም እንዲሁም የወለድናቸው ልጆቻችን አለጥቅም አይወዱንም ስለዚህ በዚህም ምድር ላይ በቀጥተኛም ሆነ በተዘዋዋሪ መንገድ ሰዎችን የምንወደው ከምናገኘው ጥቅም የተነሳ ነው። ብዙዎቻችሁ ምን ማለቱ ነው? እኔ ሰውን የምወድው ለጥቅም ነው ማለት ነው? ሌላውስ ይሁን እናቴን? እንዴት የወለድኩት ልጄ ለጥቅም ብሎ ይወደኛል? ምንድነው ይሚያወራው እንደምትሉ አልጠራጠርም ምክንያቱም ስለዚህ ነገር ስመረምር እኔም ከራሴ ጋር ተኳርፌ ነበርና ሁላችሁም የምለውን ነግረ በጥሞናና ጽፈፌነዕ በመረዳት መንፈስ ካነበባችሁት የምናገረው ወይም ማለት የፈለኩትን በስነሥርዓት መረዳት ትችላላችሁ ማለት ነው መልካም ንባብ።

እስቲ እራሳችሁን መርምሩ ለምሳሌ እናቶች ወይም አባቶች ልጆቻችሁን ከነሱ ከምታገኙት ጥቅም የተነሳ ነው። የምተወዱት ያልኩበትን ላስረዳችሁ ለምሳሌ ገና ለገና በመውለዳችሁ ለመከበር ፈልጋችሁ፣ ልጆቻችን አድገው አንድ ነገር አየደርጉልናል ብላችሁ፣ ጧሪ ቀባሪ አለን ብላችሁ፣ ቢቸግራን ከጎናችን አይርቁም በመከራ ቀን ከአጠገባችን ይሆናሉ ብላችሁ፣ ዘራችሁ በምድር ላይ ጠፍቶ እንዳይቀር በነሱ ምክንያት የመኖራችሁ ተስፋ በመሆናቸው፣ ሲያገቡ ሲመረቁ ሲወልዱ የነሱ ደስታ የናንተ ደስታ ስለሆነ እንዲሁም በህይወት መኖራቸው ስለሚስደስታችሁና ውስጣችሁ ከዛ ደስታ የተነሳ ስለሚጠቀም የመኖራቸውም ምስጢር ትቅም ነው ማለት ነው።  እነዚህ ሁሉ ለቤተሰቦች ልጆቻቸውን ለመውደድ እንደምክንያት አርገን ልንጠቀምባቸው እንችላልን። 

እንዲሁም ልጆች ቤተሰቦቻቸውን የሚወዱበት የተለያየ ምክንያት አለ ከነዛም ውስጥ ወልደው ስላሳደጓቸው ስለሚንከባከቧቸው በችግር በመከራ ጊዜ ከጎናቸው ስለማይለዩ በጨንቃቸው ቢጠባቸው የሚፈልጉትን ነገር ከማንም በበለጠ ሁኔታ ከነሱ ማግኘት ስለሚችሉ ጠዋት ማታ ስለሚጨነቁላቸውና በዚህ ምድር ያለው ጥሩ ነገር ሀሉ የነሱ እንዲሆን ስለሚጥሩላቸው የፍላጎታቸው መሟላት ሲበዛ መውደዳቸው ይበዛል በተጨማሪም ምንም እንካን ባያደርጉላቸው በህይወት ከጎናቸው መኖራቸው ለነሱ ብርታት ነውና ያንን ብርታት በነሱ ስላገኙ ተጠቀሙ ማለት ነው አሁንም ወውደዳቸው በጥቅም ላይ የተመሰረተ ነው ማለት ነው። ብዙ መጻፍ ይቻላል ከብዙ በጥቂቱ ይሄንን ይመስላል።

ባል ለሚስ ሚስት ለባል ያለው ፍቅርስ በምን መንገድ በጥቅም ላይ የተመሰረተ ይሆናል? እሱም ልክ እንደ ሌላው በጥቅም ዙሪያ ነው።  ለምሳሌ ሚስት ባሏን የወደደችእው ከሱ በምታገኘው የተለያዩ አይነት ጥቅሞች ሊሆን ይችላል እንደሂም ባል ሚስቱን እሷን የፈለጋት ለተለያዩ አይነት ጥቅሞች ይሆናል።  እንደው መጀመሪያ እንካን ሲተዋወቁ በመተያየት ብቻ ተዋደው ነው ከተባለ እሱ እሷን በማየት እሷ እሱን በማየት ተደስተዋል ስለዚህ ሁለቱም ውስጣቸው ተጠቅሟል ማለት ነው። ስለዚህ ከመተያየት አንስቶ እስከ አብሮ መኖር ኪዚያም ወውለድ ማርጀት መሞት ደርስ ወደድንም ጠላንም ህይወታችን በተለያዩ መንገዶች በጥቀም ላይ የተመሰረተ ይሆናል ማለት ነው።

የጓደኛማቾች ፍቅር ልክ እንደሌሎቹ በጥቅሙ ዙሪያ ተጀምሮ በጥቅም ዙሪያ የሚያልቅ ነው።  አንዱ አንዱን የሚወደው ሲያደርገልት ወይም ሲያስደስተው እንደመሆኑ መጠን በጣም የምንወዳቸው የምንላቸውን ጓደኞቻችንን በምን ምክንያት በጣም እንደወደድናቸው እንመርምር በእርግጥ በግልጽ በሚያደርጉልን ነገር ብቻ ላይሆን ይችልላል ለኛ ባላቸው ጥሩ አስተሳሰብ ሊሆን ይችላል ክፉ ባለመሆናቸው ሊሆን ይችላል።  ምንም ሆነ ምንም አንዱን ከአንዱ አብልጠን ይምናይበት የጥቅም ሚዛን አለ በዛ በጥቅም ሚዛን ላይ መዝነናቸው ሚዛናቸው የደፉተን በጣም የምንወዳቸውንና የምናቀርባቸው አርገን እንናገራለን ነገር ግን እንደዛ የወደድናቸው አለጥቅም እንዳልሆነ እራሳችንን ባሀሰት ለማሳምን እንሞክራልን ምንክንያቱም ወስጣችን እውነቱን መቀበል ስለማይፈልግ ብቻ ነው። 

ስለዚህ በዚህ ምድር ላይ እንዲሁ የወደደን የሚወደን ጌታ አንድ አምላክ ብቻ ነው።  ከዚያ ውጪ ማንም ሆነ ማንም እንዲሁ አይወደንም እኛም አንወድም።  እራሳችሁን መርምሩ ስንት ቀን የኔ ያላችሁት ሰው አንድ ቀን ሲበድላችሁ በደሉ ከተሰማችሁ ፍጹማን አይደላችሁም ማለት ነው ሰዎች ናችሁ ስሜታችሁ ሊያዝን ይችላል ደሞም ያዝናል ነገር ግን እግዚአብሄርን እዩት እየገደልነው አፈቀረን እየጠላነው ወደደን እየሸሸነው ቀረበን። ከፍቅር በላይ ፍቅር ለዛውም እውነተኛ ዘላለማዊ ፍቅር ማለት ይሄ ነው unconditional love ማለት ከጌታ የምናገኘው ብቻ ነው።  ነገር ግን ያፍቅር ለኛ አልሰጠንም ማለት አልችልም አልተጠቀምንበትም ለማለት እንጂ።  መክንያቱም ጌታ እነደራሱ አርጎ ከሰራን ያንንም ይዘን ነው የተፈጠርነው ማለት ነው ነገር ግን የተሰጠንን ስጦታ በጥቅም ስለለወጥነው እውነተኛ ፍቅር ዘወትር ስንራብና ስንጠማ እንኖራለን ማለት ነው።  በዚህም ምክንያት ተወለደን አድገን ገልምሰን አርጅተን እስክንሞት ድረስ በጥቅም ፍቅር ሕይወታችን ያልፋል ማለት ነው።  እንዲሂሁም ከሞትን በኋላ ዓለም የሚያስታውሰን ስለማንነታችን ነው ያ ማንነታችን ደሞ በህየወት እያለን የነበረው ማንነታችን ነው። በሱም በአንድ ወቅተ በቀጥተኛም ሆነ በተዘዋዋሪ መንገድ እነዛን ሰዎች ጠቅመናቸው ነበር ማለት ነወ።

ይቆየን King Nafkote2/16/11

ብፁዕ አባታችንን አቡነ ዜና ማርቆስ

ብፁዕ አባታችንን የአቡነ ዜና ማርቆስ
 የብፁዕ አባታችንን የአቡነ ዜና ማርቆስን እረፍት ምክንያት በማድረግ በነጸብራቅ መጽሔት ልዩ እትም ላይ ባለፈው ዓመት ከወጡ ጽሑፎች

የቅዱሳን ጻድቃን ሕይወት በፍጹም ሃይማኖት ተመሥርቶ በቅድስና ለእግዚአብሔር የተሰጠ በመሆኑ አምላካቸው እግዚአብሔርም ልዩ ሥራውን የሠራበት፣ ኃይሉን ያሳየበት፣ በረከቱን ያስተላለፈበትና ክብሩንም የገለጠበት ታላቅ ሕይወት መሆኑን መጻሕፍት አምላካውያት በመተባበር ይመሰክራሉ። ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን በቅዱሳን ሕይወት በዝቶ የተትረፈረፈውን ይህን አምላካዊ ጸጋ ሲገልጡም “ሰብእ ይቄድሶ ለመካን፥ ወመካን ይቄድሶ ለሰብእ፤ ሰው ቦታን ይቀድሳል፣ ያከብራል፥ ቦታም ሰውን ይቀድሳል፣ ያከብራልም” ብለዋል። በዚህም ቃል መሠረት መላ ሕይወታቸውን ለመንፈሳዊ አገልግሎት የሰጡት ታላቁ ኦርቶዶክሳዊ የበረከትና የትሩፋት አባት ብፁዕ አባታችን አቡነ ዜና ማርቆስ የረገጡት ቦታ ተቀድሶና ከብሮ፣ የጨበጡት ሁሉ ተባርኮ፣ የተናገሩት ቃል ተሰምቶ እግዚአብሔር ሥራቸውን ፍጹም ስለባረከላቸው የሲያትል መካነ ብርሃን ቅዱስ ገብርኤልን ፍጹም አከበረው። በመሆኑም በኢትዮጵያውያን ኦርቶዶክሳውያን ዘንድ ሲያትል የሚታወቀው በቦይንግ ወይም በማይክሮሶፍት ማዕከልነቱ መሆኑ ቀርቶ በታላቁ ሐዋርያ በብፁዕ አቡነ ዜና ማርቆስ ሀገረ ስብከትነቱ ሆነ።
ይህንንም ልበ አምላክ ቅዱስ ዳዊት ሲገልጽ “እስመ ሠምሩ አግብርቲከ ዕበኒሃ፤ ወአክበርዎ ለመሬታ፤ ባሪያዎችህም ድንጋዮችዋን ወድደዋልና፥ መሬትዋንም ፈጽመው አክብረዋልና” (መዝ. 10114) ብሏል። በዚህ አጋጣሚ ሳልጠቅስ የማላልፈው ዐቢይ ነጥብ ብፁዕነታቸው በሲያትል ዋሽንግተን ባደረጉት ታላቅ ሐዋርያዊ ጉዞና በዜና አበው ትምህርት ከሦስቱ የቀጰዶቅያ አባቶች መካከል አንዱ በሆነው በቅዱስ ጎርጎርዮስ ዘኑሲስ (335-395 ዓ.ም) ሐዋርያዊ ተልዕኮ መካከል ያለውን ትሥሥር ነው። ይኸውም ስመ ጥር የነበረው ታላቁ ኦርቶዶክሳዊ ሊቅ ቅዱስ ባስልዮስ ዘቂሣርያ ወንድሙን ቅዱስ ጎርጎርዮስን ኑሲስ በተባለችው ትንሽ ከተማ ጳጳስ አድርጎ ሲመድበው “እኔ የምፈልገው ወንድሜ በመንበረ ጵጵስናው ዕውቅናና ማዕርግ እንዲያገኝባት አይደለም። ይልቁንም አስቀድሞ አትታወቅ የነበረችውን ኑሲስን ተገቢውን ዕውቅና ማዕርግ እንዲሰጣት ነው እንጂ” ሲል ተናግሮአል። ስለሆነም የብፁዕ አቡነ ዜና ማርቆስ መንበረ ጵጵስና ለመሆን የተመረጠችውና የታደለችው የሲያትል ከተማም ይህ የቅዱሳን አበው ታሪክ ስለተደገመባት ለብፁዕነታቸው ታላቅነት ሕያው ምስክር ነው።

በጣዕመ ትምህርቱና በሁለንተናዊ ሕይወቱ ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን መብራት የሆነው ታላቁ ሐዋርያ ቅዱስ ጳውሎስ “ተዘከሩ መኳንንቲክሙ ዘነገሩክሙ ቃለ እግዚአብሔር፤ ወእንዘ ትሬእዩ ሠናየ ግእዞሙ ወተመሰሉ በሃይማኖቶሙ፤ የእግዚአብሔርን ቃል የተናገሩአችሁን ዋኖቻችሁን አስቡ። የኑሮአቸውንም ፍሬ እየተመለከታችሁ በእምነት ምሰሉአቸው” (ዕብ. 137) ሲል እንዳስገነዘበው የብፁዕ አባታችን ሁለንተናዊ ሕይወታቸው በሚገባ የተተረጎመና ዘወትርም የሚነበብ ሕያው መጽሐፍ ነው። በመሆኑም የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻቸው የሆንን ሁላችን ብፁዕነታቸው በቃል ያስተማሩንንና ከመልካሙ የሕይወታቸው መጽሐፍ ያስነበቡንን ሃይማኖታዊ ዓላማና መንፈሳዊ ተግባር ዘወትር ልንከተልና ትተውልን የሔዱትን ታላቅ መንፈሳዊ አደራም እስከ መጨረሻው ድረስ አጽንተን ልንጠብቅ ይገባል።

በተለይም ብፁዕነታቸው በዚህ አስቸጋሪና ፈታኝ ዘመን ክርስትናን በቃል ገልጸው ያስተማሩንና በሕይወትም ተርጉመውና አጉልተው ያሳዩን ታላቅ መንፈሳዊ አባታችን በመሆናቸው መንፈሳዊ በረከታቸውን ያገኙና ጣዕመ ረድኤታቸውንም የቀመሱ ሁሉ “እግዜር በምድር” እያሉ የብፁዕነታቸውን ታላቅነትና ክቡርነት በአንክሮ ይገልጻሉ። እንደሚታወቀው በጥንቷ ቤተ ክርስቲያን ቅዱሳት መጻሕፍት ከመናፍቃን መጻሕፍት ተለይተው የሚታወቁትና መንፈሳውዊነታቸውና ደግነታቸውም የሚረጋገጠው በሦስት ዐበይት መስፈርቶች አማካይነት ነበር። እኒህም ምስክሮች ውኃ፣ እሳትና ድውያን ናቸው። ይኸውም ይታወቅ ዘንድ መጽሐፉን ከውኃ ላይ ይጥሉታል፣ ከእሳት ውስጥ ይጨምሩታል፣ ከድውያን ላይ ያኖሩታል። ከዚያም መጽሐፉ ውኃው ሳያበላሸው፣ እሳቱም ሳይበላው ደኅና ሆኖ ሲገኝ፤ እንዲሁም ሕሙማን በመጽሐፉ አማካይነት ረድኤተ እግዚአብሔር ደርሷቸው ሲፈወሱ የመጽሐፉ ደግነት ይረጋገጣል። ክቡር ዳዊት “አኅለፍከነ ማዕከለ እሳት ወማይ፤ ወአውጻእከነ ውስተ ዕረፍት፤ በሚያቃጥለው እሳትና በሚያሰጥመው ውኃ መካከል በክንፈ ረድኤትህ ጋርደህ፣ በጽላሎተ ረድኤትህ ከልለህ አሳለፍከን፤ ወደ ዕረፍትም አወጣኸን” (መዝ. 6512) እንዲል።

በዚህም መሠረት የብፁዕ አባታችን አቡነ ዜና ማርቆስም ደገኛ አባትነት ለዘመናት በብዙ ዓይነት ገድል ተፈትኖ የተረጋገጠ ከመሆኑም በላይ በብፁዕነታቸው ጸሎትና ቡራኬ የተፈወሱና የተጽናኑ ምእመናን ሥፍር ቁጥር የላቸውም። ይህም አምላካዊ በረከት በዓረፍተ ዘመን የማይገታ በመሆኑ ብፁዕነታቸው በሕይወተ ሥጋ ሳሉ ሲያስተላልፉት የነበረው አምላካዊ ጸጋና በረከት ዛሬም በዐጸደ ነፍስ ሆነው ሳይቋረጥ ዘወትር የሚተላለፍ መሆኑ እሙን ነው። መጽሐፍ “ወይእዜኒ ዕበዩ ለክርስቶስ በሥጋየ እመኒ በሕይወትየ ወእመኒ በሞት፣ አሁንም በሕይወትም ብሆን በሞት የተሰጠኝ የእግዚአብሔር ጸጋ ሁልጊዜ ከእኔ ነው።” (ፊል. 120) እንዲል።

በመጨረሻም ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት “ዝክረ ጻድቅ ለዓለም ይሄሉ፤ የጻድቅ መታሰቢያ ለዘላለም ይኖራል” (መዝ. 1116) ብሎ እንደመሰከረው እውነተኛው ኦርቶዶክሳዊ ሐዋርያ ታላቁ አባታችን ብፁዕ አቡነ ዜና ማርቆስ ለዘላለም ሕያው በመሆናቸው በቅዱሳን አብርሃም፣ ይስሐቅና ያዕቆብ እቅፍ ሆነው ዛሬም ይባርኩናል፣ በጸሎታቸውና በረድኤታቸውም ዘወትር ይራዱናል።

አምላከ ዜና ማርቆስ የብፁዕነታቸውን በረከትና ረድኤት በሁላችን ላይ ያሳድርብን። አሜን! (A.S)